የአንድን ሀገር ዘላቂ ሰላም እና እድገት ለማረጋገጥ የወጣቶች ሁለንተናዊ ተሳትፎ እና ተጠቃሚነት መሰረታዊ ነው፡፡ በኢትዮጵያ 70% ያህሉ ወጣቶች በመሆናቸው በሀገር እና ሀገረ-መንግስት ግንባታ እንዲሁም በሠላም እሴት ግንባታ ላይ ባላቸው ሚና በማህበረሰቡ ውስጥ ልዩ ስፍራ ይሰጣቸዋል፡፡ ወጣቶች የሚጠበቅባቸውን ሚና በአግባቡ ተረድተው ታሪካዊና የዜግነት ሃላፊነትን መወጣት እንዲችሉ በማህበራዊ፣ በኢኮኖሚና በፖለቲካ ሁኔታዎች ላይ ግልፅ ግንዛቤ ኖሯቸው እና የሚጠበቅባቸውን እንዲወጡ ማድረግ ይጠበቃል፡፡
ሰነዱ ከሀገራችንን ወጣቶች ታሪካዊና አሁናዊ ሁኔታዎች በመነሳት ከወጣቱ የሚጠበቁ ሀገራዊ ሀላፊነቶችን በዝርዝር ያስቀምጣል፡፡ ከዚህ አንፃር ወጣቶች በሀገር ግንባታ፣ በሰላም ግንባታ፣ በብሄራዊነት ገዢ ትርክት ግንባታ እና በሚዲያ አጠቃቀም ላይ ስለሚኖራቸው ሚና በሰነዱ ውስጥ ተካቷል፡፡
በመሆኑም በሁሉም የወጣት አደረጃጀቶች ያሉ ወጣቶች በሰነዱ ላይ በጥልቀት እንዲወያዩና ተቀራራቢ የሆነ ግንዛቤና አመለካከት ደረጃ ላይ እንዲደርሱ እንዲሁም ሚናቸውን እንዲወጡ ለማስቻል ይህ የውይይት መነሻ ሰነድ ተዘጋጅቷል።